top of page

የኦሮሞ ልሒቃን ያወጁት የአማራ ዘር ማፅዳት እና የዘር ማጥፋት እድገት ፤

Updated: Sep 4, 2023

የኦሮሞ ልሒቃን ያወጁት የአማራ ዘር ማፅዳት እና የዘር ማጥፋት እድገት ፤ የኦሮሞ ብሔርተኝነትን አንስተው ያንቀሳቀሱ የኦሮሞ ልሒቃን የነፃነት ግንባር መሥርተው ከተንቀሳቀሱ በዚህ አመት 50 ዓመታት ሞልቷቸዋል።

የዚህ ብሔርተኝነት መነሻ ፣ ሒደቶቹ ፣ ያስገኛቸው ውጤቶች እና ድክመቶች የሚሉ አመክንዮያዊ ጉዳዮች ለአካዳሚክ ዘርፍ ሙያተኞች እንተወውና ፥ ያ ብሔርተኝነት እና የዛሬው የኦሮሞ ልሒቅ ፖለቲካ እንዴት ወደአማራ ዘር ማፅዳት አደገ የሚለውን ሒደቶች እና ልሒቃኑ የሚገኙበትን የዘር ማፅዳትና ዘር ማጥፋት ቁመና እንመልከተው።


በኢትዮጵያ የፀረ-አማራ ትርክቶች እድሜ ሁለት ትውልድ ተሻግሯል። ከ20ኛው ክፍለዘመን ኤምፔሪያሊስት ቅኝ ገዢዎች እስከ 1960ዎቹ የብሔር አቀንቃኝ ድርጅቶች ፀረ-አማራነትን በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ በፖለቲካ መርህነት አራምደዋል። እንደሕወሓት/ወያኔ ያሉት ትርክታቸውን ባገኙት ስርዓታዊ ቁጥጥር በተግባር ለመበቀል ሠርተውበታል። የአማራ ሕዝብን ማዕከል አድርጎ በተሰበከው የጥላቻ ስሁታዊ ትርክት ሕዝባችንን ካለፉት 30 ዓመታት መዋቅራዊ ሥሪት ተደርጎ እና መንግስታዊ ድጋፍ ያለው ሁሉን አቀፍ ፍጅት እየተፈጸመበት ይገኛል።


ወያኔ፥ አማራን የመቀነስና ሆን ብሎ የመግታት ታሣቢነት በዘረጋው ሥርዓት ሁለት አይነት አማራን በመፍጠር ነው የሠራበት። አማራ ክልል ብሎ በሠራው ክልል የሚኖር እና በመላ ኢትዮጵያ የሚኖር በሚል ሰፊውን አማራ፡ ባለቤት አድርጎ በሰጣቸው የጎሳ ቡድኖች ስር እንዲሆን አደረገው።

በመላው ኢትዮጵያ የሚኖረው አማራ በዘላቂነት የጥቃት ኢላማ ሆኖ እንዲኖር የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን እጣ ፈንታው መጥፋት ብቻ እንዲሆን አድርጎ ሠራው።

ስርዓቱ ለሌሎች የሠጣቸውን መብቶች በመንፈግ ለጥፋት አመቻችቶ ሠጥቶታል።

በኦሮሞ ልሒቃን ዘንድ ደግሞ << ቅኝ ተገዝተናል ፥ በሠፋሪ ቅኝ ግዛት ተገዝተናል>> የሚሉ ትርክቶች ረጅም ጊዜ ያስቆጠሩ ናቸው። እነዚህ በኦሮሞ ብሔርተኞች ሲሰበኩ የቆዩ አሉታዊ ትርክቶች በወያኔ ስሪትና እርምጃዎች ላይ ጎምርተው የበቀሉ በመሆናቸው ትርክቶችን አስከትለው በሚፈፀሙ ልዩ ልዩ የዘር ማጥፋት ገፅታዎች የሚበየኑ ናቸው ።


የኦሮሞ ልሒቅ አማራውን በተመለከተ ሲያራምዳቸው የኖሩ ትርክቶች የዘር ማጥፋት ተግባርን ወልደውለታል። በተለያየ ገፅታቸው የሚገለጡ የዘር ማጥፋት አይነቶችን ከትርክት እስከ ተግባር እየፈፀሙ ይገኛሉ።

የባሕል ዘር ማጥፋት (Cultural genocide) ፣ የኢኮኖሚ ዘር ማጥፋት (economic Genocide) ፣ የአማራ ማንነት ዘር ማፅዳት እና ዘር ማጥፋት (Ethnic Genocide and Ethnic cleansing) ፣ እንዲሁም የስነ-ሕዝብ አኃዛዊ ዘር ማጥፋት (statistical genocide) ፣ አእምሯዊ ውድመት (Intellectual genocide) ፥ ወዘተ የኦሮሞው ልሒቅ፥ በአማራ ሕዝብ እና አማራነት ላይ እየፈፀማቸው የኖሩ እና የቀጠሉ ጥቃቶች ናቸው።

በእነዚህ አምዶች፡ አማራው ላይ የተሠሩ ትርክቶች እና የደረሱ ማጥፋቶችን በተመለከተ ተከታታይ ትረካዎችን እናቀርባለን።

ለዛሬ የአማራን ባሕል እና ታሪክ ማጥፋት (Cultural genocide) የተመለከተውን ሐተታ እንመልከት።


የባሕል ዘር ማጥፋት ሲባል የአንድን ሕዝብ መገለጫዎች፣ ባሕል፣ እሴቶች፣ ምልክቶች፣ ማጥፋት ነው።

ምሁራን የባሕል ዘር ማጥፋትን በተለያየ መልኩ ተርጉመውታል። በባሕል ዘር ማጥፋት ላይ ተፅፎ Jeffrey S. Bachman በተባለ ምሁር አርታኢነት የወጣ መፅሐፍ ላይ እንደተጠቀሰው ፥ የባሕል ዘር ማጥፋት ሲባል የአንድን የሚፈሩትን ቡድን (ማንነት) ባሕላዊ እሴቶች እና ተግባሮች ሆን ብሎ ማዳከም እና ጨርሶ ማጥፋት ነው። (“the purposeful weakening and ultimate destruction of cultural values and practices of feared out-groups;”)

እንደዚሁም ሌሎች ታሳቢ አላማዎችን ለማሳካት ሲባል ሆን ተብሎ ወይም በአጋጣሚ የአንድን ማሕበረሰብ መገለጫዎችና የሕይወት ትርጉም የሚሠጡ የእሴት ስርዓቶች እና ባሕላዊ አንድነት ማጥፋት፣ መሸርሸር፣ ማሳነስ ይለዋል።

የኦሮሞ ዘረኛና ፅንፈኛ ልሒቅ ፥ ዘር አጥፊነትን የተላበሰ ብሔርተኝነትን ሲጀምር፥ "ቅድሚያ ኦሮሞ - Oromo first" በሚል እየተቀነቀነ በብዙ መልኩ ሲገለፅ የኖረ እና "ሌላ-ጠልነትን" ተላብሶ ሲተረክ የኖረ ነው። "ኢትዮጵያ ከኦሮሚያ ትውጣ" የሚል ቅስቀሳ ሲሠሩ የነበረው የዘር ማጥፋት እና የባሕል ዘር ማጥፋት መንደርደሪያቸው ነበር።

የኦሮሞ ልሒቃን በአማራው ላይ የሚፈፅሟቸው የባሕል ዘር ማጥፋት ተግባራት አላማዎች ፥ "በኦሮሞ መገለጫዎች እንደገና የምትሠራ ኢትዮጵያን" እውን ማድረግ ነው።

ይሔን ለማድረግ ደግሞ የራስን ባሕል፣ ቋንቋ፣ ታሪክና ቅርስ ወዘተ ከማልማት ይልቅ ፣ የሌላውን ማጥፋትና ማሳነስ አላማ አድርጎ የሚሠራ ልሒቅ ነው። እነሱ ይሔንን መልሶ-ብየና (Deconstruction) አስፈላጊ ጉዳይ አድርገው የማውደም ተልዕኮ ውስጥ ገብተዋል።

ይሔ መልሶ-ብየና ሌላውን በተለይም አማራውን ማውደም ሆኗል። "የአቢሲንያ ባሕል ነው" የሚሉትን መጠየፍ የልሒቃኑ መገለጫ ነው። የባሕል ዘር ማጥፋት ሲባል የአንድን ሕዝብ ቋንቋ፣ ኃይማኖት፣ ባሕል የማጥፋት፣ የማራከስ፣ የማሳነስ፣ ፍላጎት፡ ተነሳሽነት እና ተግባር ነው።


ይሔም ፦


1) የቡድኑን ቋንቀቀ በቀንተቀን ንግግሮች ወይም በትምሕርት ቤት እና በሌሎች የመገናኛ መንገዶች ቋንቋውን ከመጠቀም መከልከል፥


2) የተፈራውን ወይም ትኩረት የተደረገበትን ሕዝብ መገለጫዎች በየትኛውም ሁኔታ ጥቅም ላይ እንዳይውል ማድረግ ነው። ከቤተ-መፅህፍት፣ ከሕዝብ አገልግሎት ተቋማት ከእምነትና ማሕበራዊ አገልግሎት መስኮች ሁሉ ማገድን ይመለከታል።


የዚህ አስተሳሰብ እና እንደባዕድ የማየት መነሻ የኦሮምኛ ቋንቋን የፅሑፍ ፊደል ከሳባ ወደ ላቲን በመቀየር አሳይተዋል። አንድ ቡድን የፈለገውን ቋንቋ እና ፊደል የመጠቀም መብቱ እንደተጠበቀ አናጣውም፤ የእነዚህኞቹ መነሻ ግን "የሰሜን" ላሉት ፊደል ያላቸውን ጥላቻ ማሳያ ነው።


ሰዎቹ ከፊደል ለውጡም በላይ ለአማርኛ ቋንቋ ያላቸውን ጥላቻና የማጥፋት ፍላጎት አልደበቁንም። በልሒቃኑ ፋሽስቶች በኩል "የእኔ" ያሉትን ቋንቋ ለማሳደግ፥ የሌላውን የማጥፋት አስፈላጊነት የክፋት አላማቸውን ገልፀዋል። ክልሉን እንዲመራ የተቀመጠው ሽመልስ አብዲሳ በአንድ ወቅት አማርኛን እየሞተ ነው በማለት የጥላቻ እርሙን አሰምቶ ነበር።

ንግግሩን እንጥቀሰው፥

" አፋን ኦሮሞን የተመለከተ አንድ ዳታ ልስጣችሁ። በ87 አፋን ኦሮሞ በ12 በ13 % ከአማርኛ በታች ነበር። አሁን አፋን ኦሮሞ ኢትዮጵያ ውስጥ አማርኛን ከ 10% በላይ ይበልጠዋል። የአማራን ብሄር አላልኩኝም እኔ አፋን ኦሮሞ በተናጋሪ አማርኛ ቋንቋ ይበልጣል ነው ያልኩት። አማርኛ ነው አፋን ኦሮሞን በተናጋሪ ብዛት የሚበልጠው ብላችሁ ካሰባችሁ ትልቅ ስህተት ውስጥ ናችሁ። ቤንሻንጉል 37% አፋን ኦሮሞ ይናገራል፣ ጋምቤላ፣ ሃረሪ፣ ሶማሌ ውስጥ፣ ነው ያልኩት። አማርኛ እየሞተ ነው የመጣው፣ ወደታች ነው እየሄደ ያለው።"

ይላል አቶ ሽመልስ።

"አማርኛን ለማሳነስ እና ኦሮምኛን ለማስፋት እየሠራን ነው" ከሚለው የሽመልስ አብዲሳ ፉከራ ውስጥ ፀረ-አማራነትን ለመደበቅ አይታገሉም። "አማርኛን ከአስተዳደራዊ ቀጠናቸው ለማጥፋት የሚሠሩትን ያሕል የሌላው አጋር መስለው "ኦሮምኛ ቋንቋን አስተምሩ" ተብለው የሚገደዱና የሚሠበኩ ሌሎች ክልሎችም አሉ።

"ኦሮሚያ" ያሉትን ክልል፣ ከአማርኛ ቋንቋ ለማፅዳት የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል። ከ10 ሚሊዮን የሚልቀው አማራ፥ "የኦሮሞ" በተባለ ክልል የሚኖር በመሆኑ ብቻ በራሱ ቋንቋ የመጠቀም መብቶቹ ተነፍጓል። እናም ገዢዎቹ የጫኑበትን ቋንቋ የመጠቀም ግዴታ ውስጥ ከተውታል። ባህሉንና መገለጫውን ለማሳደግ የሚሠራበት እድል ተዘግቶበታል።


ሌላኛው የባሕል ዘር ማጥፋት ገፅታ የአንድን ሕዝብ መገለጫና ምልክቶች መከልከል፣ ማፍረስ እና ማጥፋት ነው። የኦሮሞ ልሒቃን የአማራ የሚሉትን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ቀለም በተመለከተ ያላቸው አስተሳሰብና ተግባር ከሞኝነት ያለፈ ነው። የክልሉ ሰንደቅ መቀየራቸው እና የፈለጉትን የመጠቀም መብት እንዳላቸው ሁሉ፣ ሌሎች ግለሰቦችና ቡድኖች የፈለጉትንና የወደዱትን ቀለም የመጠቀም ምልክት የማድረግ መብት እንዳላቸው አይቀበሉም። ለነገሩ ፋሺዝም ከመብትና እኩልነት እሳቤዎች ጉዳይ የለውም።


እናም ከነጠላ እና ቀሚስ ላይ ሳይቀር አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ያለበት አለባበስን ሲከለክሉ ታይተዋል። እንደጥምቀትና መስቀል ባሉ የሕዝብ በዓላት ፡ አረንጓዴ ቢጫና ቀይ ቀለም እንዲያድኑ የሚሠማሩ የስርዓቱ ታጣቂዎች ተለምደዋል። በከበሮ ገመድ ላይ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ አለበት ተብሎ ሲያስፈቱ ተመልክተናል።

እነሱ የፈለጉትን ቢለብሱ ዘወር ብሎ የማያያቸውን ሕዝብ፥ የምትለብሰውን ልብስ ቀለም እና ምልክት እንምረጥልህ ይሉታል። በዘር ማጥፋት ላይ የተሠማራ ፋሺዝም እንዲህ ነው !!


የባሕል ዘር ማጥፋት ሌላው መገለጫ ቅርሶችን ማጥፋት ነው። "የሌላ" ያሉትን ሐውልት አፍርሶ፥ "የኔ" የሚሉትን ሐውልት ማቆም የሒደቶቹ ማሳያ ነው!!

በኦሮሞ ልሒቅ የሚቀነቀኑ እጅግ አደገኛ ትርክቶች በአንድ በኩል ሀውልት ሲቆምላቸው አይተናል። አፄ ምኒልክ በአገር ማስፋፋት ሒደቶች ጡት አስቆርጠዋል የሚል ትርክትን ለብሔርተኝነት መቀስቀሻ ያደረጉት ልሒቃኑ "አኖሌ" ብለው ሐውልት እስከማቆም ሔደዋል።

ይሕ የሐውልት ማቆም ሥራ እንግዲህ ከ200 አመታት በኋላ በክፉ ትርክታቸው የማሕፀን ፅንስ የሚያኮላሽ ትውልድ የፈጠሩ፣ አንገት የሚቀሉ ፅንፈኞችን ያደራጁ፣ ሕፃናትና አረጋውያንን አቃጥለው የሚገድሉ ጭፍኖችን በፈጠሩ ብሔርተኞች የተፈፀመ ነው።


በተመሳሳይ ሐረርጌ "ጨለንቆ ላይ የሐረሪ ሠርገኞች በምኒልክ ሠራዊት ተጨፍጭፈዋል" በሚል ትርክት፡ ሐውልቶች በሐረርና ጨለንቆ ላይ ቆመዋል።

በሌላ በኩል ሐረር ላይ ፥ የኢትዮጵያ አገር ምስረታ ባለውለታ የልዑል ራስ መኮንን መታሠቢያ ሐውልት ሲፈርስ ፣ ለመታሰቢያቸው ቆመው የነበሩ ተቋማት የስም ለውጥ ተደርጓል። የራስ መኮንን አዳራሽ ወደ አሚር አብዱሊሒ አዳራሽ ተቀይሯል። ሌሎች ትምህርት ቤቶችም እንዲሁ ስያሜያቸው ተቀይሯል።

የዘር ማጥፋት አስተሳሰብ እና ግብር እንደዚህ ያለ ነው። ፍትሕ የሚለው የደረተውን ትርክት ተከትሎ ሌላውን አፍርሶ የራሱን ሲገነባ ነው።

ዛሬም አዲስአበባ ፒያሳ ላይ የቆመው የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሠቢያ ሐውልት በኦሮሞ ዘረኛ ልሒቃን ዘንድ "የቅኝ ገዢ ሐውልት" ተብሎ እንዲፈርስ ቀን የሚጠብቁለት እና ዛቻ የሚያሰሙበት ነው።

"ገዳ ሜልባ" በሚል ኦነግ በ1980ዎቹ ያሳተመው መፅሐፍ ላይ ይሔንን አላማ አስቀምጧል። "በሐረር እና ፊንፊኔ ቆመው የሚገኙ ሐውልቶች፥ በሌሎች አገራት የነበሩ የቅኝ ሐውልቶች እንደፈረሱት ሁሉ ይፈርሳሉ" ይላል።

አስገራሚው ነገር፥ ኦነጋውያኑ እነሌንጮ ለታ እና ዳውድ ኢብሳ ለሀምሳ አመታት ያቀዱትን ፣ የተመኙትንና የደከሙለትን ሁሉ ፡ አብይ አሕመድ እየፈፀመላቸው መሆኑ ነው።

የሌሎችን ሐውልት ለማፍረስ የሚተጋው የኦሮሞ ልሒቅ ፡ በሐውልት ግንባታ ተወዳዳሪ እንደሌለው አሳይቷል። በአንድ አመት ከአሥር በላይ ሐውልቶችን ገንብቶ አስመርቋል።

የአድዋ ድልን "በምኒልክ አደባባይ" ማክበር በሕግ የተደነገገ ፣ የአከባበር ሥነ-ስርዓት የወጣለት አገራዊ በዓል ቢሆንም ፥ ሰዎቹ በአደባባዩ ማክበር ከልክለው፣ ቀኑን ለማክበር የሔዱ ወጣቶችን ሰብስበው አስረዋል።

ይባስ ብሎም በሥርዓቱ ተላላኪ ጀነራል አበባው ታደሰ በኩል ፡ "አፄ ምኒልክ እና ንግስት ጣይቱ ሲነሱ የማይወድ ሰው አለ" በማለት አገራዊ የድል በዓል የሆነው አድዋና የኢትዮጵያ መሥራች ነገስታትን ታሪክ የማውደም ዘመቻ አውጇል። የጥላቻቸው ልክ በሕግ "የዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ" ተብሎ የተሠየመውን ቦታ ጀነራሉን ጨምሮ "ጊዮርጊስ አደባባይ" ብለው ስም ለውጠው ሲጠሩ ታይቷል።

ይባስ ብለው የነገስታቱ ፎቶግራፎች ያለበት ሽመና ሠርታችኋል ያሏቸውን የአዲስአበባ ሽሮ ሜዳ የሽመና ሙያተኞች እስከማሠር ሔዱ።

በመንግስት ቁጥጥር ስር ያሉ የአገሪቱ ሚድያዎች የአፄ ምኒልክን እና ንግስት ጣይቱን ፎቶ ግራፍ እንዳያሳዩ በተከለከለበት የአድዋ በዓል አከባበር ፤ የአገሪቱ የባሕል ሚኒስትር የተደረገው የኦነግ አመራር ቀጀላ መርዳሳ ደግሞ የአብይ አሕመድን ፎቶ ከባልቻ አባሳፎ ፎቶግራፍ ጋር አሠርቶ በመስቀል አገራዊ በዓል አከባበር አደረገ። በመጪው በዓል ደግሞ ወይ በዓሉን ማክበር ይከለክላሉ ወይም እንደዛቱት ሐውልቱን ለማፍረስ ይነሳሉ።

"ታሪክ የሌለው ሕዝብ፥ ታሪኩንም የማይዘክር ሕዝብ ታሪክ አይሠራም ነውና ብሒሉ፣ እየተፈፀመ ያለው፥ ታሪክ በማጥፋት፡ ታሪክ አልባና ታሪክ የማይሠራ ሕዝብ ፡ የመፍጠር ዘር ማጥፋት ነው። የታሪክ ሥርዓተ-ትምሕርት እሰጥአገባ የምናስታውሰው ነው። አላማው የአንድን ቡድን ታሪክ ለማንገስ የሌላውን ማንኳሰስና ማጥፋት መሆኑ ነው።

ይሔው የቅርስ ውድመት እና ትዝታን በማጥፋት የባሕል ዘር የማጥፋት አላማ በተለይ በአዲስአበባ ተጠናክሮ ቀጥሏል። በአዲስአበባ የኮተቤ ዩኒቨርሲቲ መምሕር የሆኑት ዶር በቃሉ ፥ በአዲስአበባ የባሕል ዘር ማጥፋት (cultural genocide) እየተፈፀመ መሆኑን በአንድ ቃለመጠይቅ ፅፈዋል። በአዲስአበባ ውስጥ የሚታወቁ ቅርሶች ፣ የከተማዋና የአገሪቱ ምልክቶች የሆኑ በርካታ ተቋማትና ኪነ-ሕንፃዎች እንዲፈርሱ ተደርገዋል። ታሪካዊውና የመጀመሪው ሲነማ ቤት (ሰይጣን ቤት) በተደጋጋሚ ለማፍረስ ሲሠራ ቆይቷል። በሕዝብ ጩኸት እስከዛሬ ሕልውናው አለ። ሌሎች የአዲስአበባ ነባር መንደሮች እና ኪነ-ሕንፃዎች ከትዝታ ተፍቀዋል።


የኦሮሞ ልሒቅ በአማራ ላይ ያወጀው የዘር ማጥፋት አንዱ ገፅ የሆነው የባሕል ዘር ማጥፋት (Cultural Genocide) አይነተ-ብዙ ነው። አማራውን እና የአማራ የሚሉትን ማሳነስ ፣ የእኔ የሚሉትን ባሕልና መገለጫ ለማሳደግ የሚደረግ የዘር ማጥፋት ተልዕኮ ነው።


አሳዛኙ ነገር ግን ይሔንን ግፍ አብሮ ተሰልፎ እያስፈፀመ ያለው የአማራ የፖለቲካ ኃይል መሆኑ የመጥፋት ሒደቱ አሳዛኝ ገፅታ ነው። የአማራ ብልፅግና እና የአብን አመራር ይሔንን ጥፋት ከሚፈፅም የኦሮሞ ልሒቅ ጋር ተሰልፏል።

ለባሕል ልማት ቅርበት የነበራቸው፣ ሊቆረቆሩ ይችላሉ ተብለው የሚታሰቡ የአማራ ልሒቃን በአገዛዙ ተጠልፈው ወድቀዋል።

ይባሱኑ ፊት ተሰላፊና አስፈፃሚ ናቸው። ታሪክና ቅርስ እየወደመ የአማራ ተወላጅ የሆነው ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው የቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ሹመኛ በመደረጉ የመቃወም ወኔው ተነጥቋል። ባሕልና እሴቶች የጥቃት ኢላማ በሆኑበት እነ ሠርፀ ፍሬ ስብሐት በስልጣን ተጠልፈው እምቢ የማለት ወኔያቸው ተገፎ (Co-opeted elites) ወድቀዋል።


የአማራውን ቋንቋ ማሳነስና ማጥፋት ፣ የአማራ ታሪክ እና ትዝታ የሚሉትን ማጥፋት ፣ የአማራነት መገለጫ የሆኑ እሴቶቹንና ባሕሎቹን ማሳነስ፡ ማንቋሸሽ፡ ማጥፋት፣ እንዲሁም ሌሎች መገለጫዬ የሚላቸውን ምልክቶቹን እና ቅርሶቹን ማውደምና ማጥፋት ላይ ያነጣጠረ ምንጠራና የማጥፋት ሥራ እየሠሩ ነው።


በሌሎች የአማራ ዘር ማጥፋት ጥቃቶች ዙሪያ ተከታታይ ዝግጅቶችን እንቀጥላለን።


በዚህ ሁሉ የጥፋት እርምጃ ውስጥ ግን ሰፊው የአማራ ምሁር ፣ የአማራ የፖለቲካ ኃይል እና የአማራ ልሒቅ ግን ይሔንን ሁሉ በማንነቱ ላይ የታወጀ ጦርነት ፡ ተቀምጦ ከመጠበቅ እና ከማየት ያለፈ ነገር ሲያደርግ አይታይም።

ምን ያለ ጥቃት ነው በጋራ የሚያቆመውና እርምጃ የሚጀምረው!? እስከመቼ መጥፋታችንን ተቀምጠን እንቆጥራለን!?



 

Disclaimer: The opinions expressed in this article are those of the authors. They do not purport to reflect the opinions or views of the Amhara Popular Front ( APF) or its affiliates.

12 views0 comments

Comments


bottom of page